አርሰናል ከኒውካስል ዩናይትድ ጋር ከሚያደርገው ጨዋታ አስቀድሞ፣ የቡድኑ መሪ ማርቲን ኦዴጋርድ ባለፈው ሳምንት በማንቸስተር ሲቲ ስለነበረው ጨዋታ፣ ስለ ዋንጫው ሽሚያ፣ ከጉዳት መልስ ስለ ጉልበቱ ሁኔታ እና ከኒውካስል ምን እንደሚጠበቅ አውርቷል። የንግግሩ ጥቂት ነጥቦች እነሆ፦
ባለፈው ሳምንት መጨረሻ በማንቸስተር የነበረው ውጤት በእውነት የሚያበሳጭ ነበር። ብዙ ጥሩ ነገሮችን አድርገናል፣ ጨዋታውን ለማሸነፍም ዕድሎች ነበሩን። በሁለት ጠንካራ ቡድኖች መካከል የተደረገ ጥብቅ እና ክስተቶች የበዙበት ጨዋታ ነበር፤ በመጨረሻም በትንሽ ልዩነቶች ተወሰነ።
በሁለተኛው አጋማሽ በጣም ጥሩ ነበርን ብዬ አስባለሁ፤ ጥቂት ግሩም አጋጣሚዎችንም ፈጥረን ነበር። በእነሱ ላይ ጫና መፍጠር ብንችልም ጨዋታውን ግን መጨረስ አልቻልንም። የተከላካይ ክፍላቸው ላይ የፈጠርነው ጫና (high press) በጣም ጥሩ ነበር፤ ጨዋታው እየገፋ ሲሄድም ወደ ግብ ክልላቸው በመድረስ አደገኛ ነበርን። ጥቂት ትልቅ ዕድሎችን ፈጥረናል፣ ኳስ ሁለት ጊዜ የግብ ብረቱን መትቶብናል፤ ነገር ግን ሁለተኛውን ግብ ማግኘት አልቻልንም፤ ጨዋታው የተወሰነውም እዚያ ጋ ነው።
በእርግጥ የምንወስዳቸው በጎ ነገሮች አሉ፤ ነገር ግን ያለ ምንም ነጥብ ወደ ቤት ስትመለስ፣ በተለይም በዚህ የውድድር ዘመን ወቅት ላይ፣ በጭራሽ ደስተኛ ልትሆን አትችልም። ስለዚህ ያንን ትተን ስህተቶቻችንን በማረም ለዛሬው ጨዋታ በጠንካራ ሁኔታ እንመለሳለን።
ሁላችንም ምን ማድረግ እንዳለብን፣ በምን ዓይነት ሁኔታ ውስጥ እንዳለን እና ምን ዋጋ እንደሚያስከፍል በሚገባ እንረዳለን። ዛሬ ያ የእኛ ዕድል ነው። በደንብ የምናውቀውን ሌላ ጠንካራ ቡድን እንጋፈጣለን፤ ስለዚህ አገግመን ጉዟችንን ለመቀጠል ትልቅ ዕድል ነው። እስከ መጨረሻው ድረስ መጓዝ እንፈልጋለን፤ የምናደርገውም ያንኑ ነው።
ትኩረታችን በእያንዳንዱ ጨዋታ ላይ ነው፤ በወቅቱ መገኘት እና በምትጫወትበት ጊዜ ሁሉ ለማሸነፍ መጣር ነው። እስከ መጨረሻው ድረስ ከባድ እንደሚሆን ሁልጊዜም እናውቅ ነበር፤ ስለዚህ የእኛ አስተሳሰብ መቀጠል ነው። ጠንክረን እየሰራን፣ ተባብረን እያንዳንዱን ጨዋታ በጉጉት እየጠበቅን ነው። ሁሉም ነገር ክፍት ነው፤ ይህ የውድድር ዘመኑ ምርጡ ክፍል ነው።
ሁላችንም ለምን እንደምንጫወት እናውቃለን፤ ሁላችንም ቁርጠኛ እና ትኩረት ያደረግን ነን። የሚደረጉ ብዙ ጨዋታዎች አሉ፤ በዚህ የውድድር ዘመን ወቅት ደግሞ ዋናው ነገር ንቁ እና ዝግጁ ሆኖ መገኘት ነው። ለምን እንደምንጫወት ስለምናውቅ ተነሳሽነት (motivation) ለመፍጠር መድከም አያስፈልግም፤ ያ ቀድሞውኑ አለ። ከዛ በኋላ አካልን እና አእምሮን ማዘጋጀት፣ መታገል እና ለቀጣዩ ጨዋታ ዝግጁ መሆን ብቻ ነው።
አሁን በሊጉ አምስት ጨዋታዎች ይቀሩናል፤ ይህ ደግሞ ጥሩ ሁኔታ ነው። ከሻምፒዮንስ ሊጉ ጋር ተዳምሮ ለእኛ ድንቅ ዕድል ነው፤ ስለዚህ በቀሪዎቹ ስድስት ሳምንታት ያለንን ሁሉ እንሰጣለን። በውድድር ዘመኑ መጨረሻ ላይ መሆን የምትፈልገው በዚህ ዓይነት ሁኔታ ውስጥ ነው፤ እኛ ደግሞ እዚያ ላይ ነን። አሁን እያንዳንዱን ቀን እና እያንዳንዱን ጨዋታ በአግባቡ መጠቀም አለብን።
በግል ደረጃ ባለፈው ሳምንት መጨረሻ 90 ደቂቃ መጫወት መቻሌ ጥሩ ስሜት ሰጥቶኛል። ሙሉ ጨዋታ ከተጫወትኩ ቆይ ስለነበር ከጨዋታው በኋላ ዝም ብዬ ነበር። በጉዳት ምክንያት ለእኔ እንግዳ የውድድር ዘመን ነበር፤ እንደምፈልገው ብዙ ጨዋታዎችን አልተጫወትኩም፤ ስለዚህ ከጨዋታው በኋላ በእርግጥም ደክሞኝ ነበር። ከዛ ውጪ ግን ጥሩ ስሜት ተሰምቶኛል፣ ጉልበቴም ደህና ነው። ከዚያ በኋላም ጥሩ ምላሽ ነበረው፤ ይህም አዎንታዊ ነገር ነው።
አሁን ሙሉ ትኩረታችን ዛሬ ኒውካስልን መጫወት ላይ ነው። የወቅቱ አቋማቸው ምንም ይሁን ምን፣ እነሱ አስቸጋሪ ቡድን መሆናቸውን እና በራሳቸው ቀን ማንንም ማሸነፍ እንደሚችሉ እናውቃለን። ያንን በብዙ ጨዋታዎች አሳይተዋል። በደረጃ ሰንጠረዡ መሆን በሚፈልጉበት ቦታ አለመሆናቸው እውነት ነው፤ ነገር ግን አሁንም በብቃት የተሞላ ቡድን ነው፤ ከእነሱ ጋር የሚደረግ ፍልሚያ ሁልጊዜም አካላዊ ጥንካሬ የሚጠይቅ እና ከባድ ነው።
አስተያየት ይስጡን