የምዕራብ ለንደኑ ክለብ ቼልሲ፣ በቅርቡ ካሰናበታቸው ሊያም ሮዜኒየር በኋላ ያለባቸውን የአሰልጣኝ ክፍተት ለመሙላት የቀድሞ አሰልጣኛቸውን ጣሊያናዊውን አንቶኒዮ ኮንቴን ወደ ስታምፎርድ ብሪጅ ለመመለስ ከፍተኛ ፍላጎት እንዳላቸው ተዘግቧል።
ቼልሲ አምስት ተከታታይ የሊግ ጨዋታዎችን በመሸነፉ ምክንያት አሰልጣኙን ያሰናበተ ሲሆን፣ በአሁኑ ወቅት ካለም ማክፋርሌንን በጊዜያዊ አሰልጣኝነት መርጧል። ይሁን እንጂ ክለቡ ለቀጣዩ የውድድር ዘመን በዓለም አቀፍ ደረጃ ስም ያላቸውንና ውጤታማ አሰልጣኝ ለመቅጠር በሚያደርገው ጥረት ኮንቴን እንደ ዋነኛ እጩ ይዟቸዋል።
እንደ ጣሊያኑ የዜና ምንጭ “ካልቺዮ መርካቶ” ዘገባ ከሆነ፣ ኮንቴ በቼልሲ በቆዩባቸው ከ2008 እስከ 2010 ዓ.ም. (እ.ኤ.አ 2016-2018) ባሉት ዓመታት ክለቡን ለፕሪምየር ሊግ ዋንጫ በማብቃታቸውና በክለቡ ደጋፊዎች ዘንድ ያላቸው ተወዳጅነት ለጥያቄው መነሻ ሆኗል።
በአሁኑ ወቅት ኮንቴ ከጣሊያኑ ናፖሊ ጋር እስከ 2019 ዓ.ም. (2027) የሚቆይ ኮንትራት ያላቸው ሲሆን፣ ናፖሊን በ2017 ዓ.ም. የሴሪ አ ሻምፒዮን ማድረግ ችለዋል። በመሆኑም ቼልሲ አሰልጣኙን ለማግኘት ከናፖሊ ጋር ከባድ ድርድርና ከፍተኛ ካሳ እንደሚጠብቀው ይገመታል።
ከቼልሲ በተጨማሪ የጣሊያን ብሔራዊ ቡድንም ኮንቴን ዳግም ለመቅጠር ፍላጎት እንዳለው ተገልጿል። ጣሊያን ለተከታታይ የዓለም ዋንጫዎች ማለፍ ባለመቻሏ፣ ኮንቴን እንደ አዳኝ እያየቻቸው ትገኛለች።
ቼልሲ በአሁኑ ወቅት ወጣትና ተሰጥኦ ያላቸው ተጫዋቾች ቢኖሩትም፣ ውጤት ሊያመጣ የሚችል ጠንካራ መሪ በመፈለጉ ኮንቴን እንደ ተመራጭ ወስዷቸዋል። ኮንቴ ወደ ቼልሲ የሚመለሱ ከሆነ፣ በቅርቡ በቶተንሃም የነበራቸውን ያልተሳካ ቆይታ በማጥፋት በፕሪምየር ሊጉ ዳግም ስማቸውን ለማስጠራት ዕድል ያገኛሉ።
አስተያየት ይስጡን